ቤባንያ ገፅ ፪

December 14, 2023

…..ልቤ የወትሮ ህብረ ዝማሬውን በብዙ ወንዶች ድምፅ የአሰማ መሰለኝ፡፡ ተናደድኩ:: ውርጭ የጠጣውን መሬት እየወገርኩ ወደ ዋናው መንገድ ለመግባት ተንደፋደፍኩ።መቼ ነው ልባችንን የዕድሜ ሙሉነት የሚረታውን ከተለከፍንበት አዙሪት የሚላቀቀው?* *በሥራ አስኪያጅነት የተሾምኩበትን የሸኖ ቅርንጫፍ ባንክ ቀርቤ አየሁት:: ለሸኖ እንግዳ በሆነ አኳኋን አሸብርቋል፡፡ ባንኩ በቅርብ ቀን እንደሚከፈት የሚለፍፈው ፅሁፍ ዋናውን መንገድ አቆራርጦ ከወዲያ ወዲህ ተሰቅሏል፡፡ አንድስ በሚያክል ድምፅ ማጉያ የአመት በዓል ዘፈን ተለቋል፡፡ ድምቀትና ጩኸት ጭምቷን ሽኖ አስጨንቋታል፡፡ ደጃፉ ላይ ቁጠማ ተጎዝጉዟል፤ ፊኛ ተሰቅሏል አነስተኛ የተጓዥ ድንኳን መልህቋን ጥላ በራሪ ወረቀቶች ይታደልባታል፡፡የተንቆጠቆጡ የባንኩ ሠራተኞች ከወዲያ ወዲህ በማለት ላይ ሳሉ አቆራርጬ ወደ ባንኩ ገባሁ፡፡ ባልኮኒውን ያልጠበኩትን አቅጣጫ ይዞ ስላገኘሁት ግራ ተጋባሁ፡፡ ከበሩ ጋር ገፅ ለገፅ ተኳኩኖ ከፋዮቿን ከውጭ እንዲታዩ የሚያጋልጥ ቦታ ሆኖ ታየኝ፡፡ተነጫነጭ፣ ተነጫነጭ የሚል ስሜት ተናነቀኝ። የቤባንያ ጦስ? እራሴን ለማረጋጋት ሞከርኩ:: ከበስተጀርባዬ ተጠግተው ከቆሙ ሰዎች እራሴን እያራቅሁ።“አንተ ምንድነህ?” አልኩ በዚህ መንገድ መተዋወቃችን እየከነከነኝ።”የገንዘብ ቤት ኃላፊ ነኝ፤ አቶ መፍትሔ” አለኝ:: ሳላውቀው እኔን ማወቁ ከነከነኝ።“አንተስ?”“የቅርንጫፉ ሱፐርቫይዘር ነኝ”“ጥሩ፤ ቀድመን መተዋወቅ ነበረብን። እኔ የሹመት ደብዳቤው የደረሰኝ ከትናንት በስተዚያ ነበር። አንዳንድ ነገሮችን ሳስጨርስ ጊዜ በማጣት በስልክ እንኳን ሳንገናኝ ቀረን…”.ምንድነው የምዘበዝበው?“ምክትል ሥራ አስኪያጁ የሉም?’ አንቱ ማለት አለብኝ?“አሁን ነው ለሻይ የወጡት”ማን እንደመለሰልኝ ልብ ሳልል ቀጠልኩ፡፡”የካሽሮቹን ባልኮኒ አቀማመጥ አልወደድኩትም። ከበሩና ከመስኮቱ ጋር ትይዩ ሆኗል፡፡ በዚህ በኩል ቢሆን ለሌሎቹ እስታፎች መቀመጫ ከለላም ይሆናል። ጨረታ የወሰደው ድርጅት ስልክ ካለ ደውሉና ንገሩት፣ ካልሆነ area manager office ንገሯቸው! የኔትወርክ ሥራ ተጠናቋል?””አዎ”“ጥሩ፣ ይሄው ነው፣ ጨርሻለሁ”ሁኔታዬ ለራሴ እየቀፈፈኝ ወጣሁ:: K. weierstrass የተባለ ሊቅ ይመስለኛል፣ ስለሒሳብ ባለሙያ ሲናገር “No Mathematician can be a complete mathematician” ብሎ ይደመድማል:: ግራ የተጋቡ እንዴት? ብለው ሲጠይቁት “unless he is also something of a poet ሲል ያክልበታል፡፡እኛ የሒሳብ ባለሙያዎች፤ ባለቅኔነቱ ይቆየንና ቅኔ በገባን‛ ስል እራሴን አሽሟጠጥኩ፡፡ ሸኖን ሳስባት ዙሪያዋ በድቅድቅ ጨለማ ይዋጥብኝና ብቻዋን በሚያጥበረብር ብርሃን ትፈካብኛለች። ሽኖን ሳያት ግን ዙሪያዋን ብርሃን ያጠራት የጋን ውስጥ ጨለማ ትሆንብኛለች፡፡

ቤባንያ ክፍል ሁለት ለማና ሰዎቹ…“ውሻው ዲዮጋን!” አልኩት የእንጨት በርሜሉ ድረስ ሄጄ። “ማነህ እውነት የተገለጠልህ? መቼም ከሽኖ አይደለህ” በበርሜሉ አፍ በኩል ስጠብቀው እንደብረት ለበስ መኪና አናቱ ላይ ባበጀው የጣሪያ መስኮት ብቅ አለ፡፡“ማነህ? ማነህ? አሸብርቀህ ደብዛዛዋን ሽኖ የተበቀልህ? የጭጋግ ዋሻዋን የለፈፍህ?…”ገናን የጠጅ ሽታ አፍንጫዬን ለበጠው።“መፍትሔ? አንተነህ? እንደ Plato ድሎት ታስሳለህ፤ እንደ ታላቁ አሌክሳንደር የገዛህ መስሎህ ትገዛለህ… ለዚህ ነው ስድባቸውን ሁሉ የወረስህ።”በርሜሉ የጠጅ ነበር ይሆን? ስል አሰብኩ፡፡ አፍንጫዬን ደፍኜ አፌን ለመክፈት ሞከርኩ፡፡”Diogenes fully challenged the authority of many famous men of his time. (Such as interrupting Alexander the Magnus himself)” አልኩት ።ቀስ ብሎ ከታንክ መተኮሻው ሾልኮ ወደውስጥ ገባና ጥቂት ካናቴራ ብቻ አድርጓል። በርሜሉ ደጃፍ ላይ ኩርምት ብሎ ተቀመጠ። የሊስትሮው ብቻ የመሰለኝ አቀማመጥ እዚህም ተደገመ፡፡“ለውሻ ለውሻ ሮም ድረስ ባልሄድክ”“እንዴት?”“እዚህ አገር`ኮ የውሻ እጥረት የለም፡፡ ያውም ከዲዮጋን ወዲህ፣ ወዲህ ብዙ የሚናቸፉ ውሾች የተመላለሱበት አገር ነው ያለን::”“ለምሳሌ?”“ውሻው አሸብርን አታውቅም?”“አላውቅም!”“የገብረህይወት ባይከዳኝ ልጅ ናቸው:: ባላንባራስ አሸብር ውሻው የተባሉ ባላባቱንና መሳፍንቱን ሁሉ ስለሚሳደቡ ‘ሳትሰሩ የምታጋብሱ አሳሞች’ እያሉ ይሳደቡ ነበር። ይሄን ጊዜ ‘ውሻው’ የሚለው ቅጥያ የማዕረግ ሥም እንደሆነ ትረዳለህ። በመጨረሻ ንጉሱንም _ አልማሯቸውም ‘ቤተ መንግሥቱን አሳማ ማርቢያ አደረጉት’ እያሉ:: በግዞት እዚህ መሃል ሜዳ እንዲቀመጡ የተደረጉት ለዚያ ነበር::””አልሰማሁም ልጄ””አትሰማም!(ስደበኝ?)ጫማዬን በመጠየፍ ተመለከተውና “ከጉልበትህ በታች ክፉኛ ቀልብ ስበሃል። ለማሰገድ ይመስላል”“እንዴት?”

“ስዎችን ከጉልበታቸው በታች ላለማየት ይቺን መስኮት ከፈትኩ፡፡ ክብሬ አይፈቅድማ! መስኮቷ ሁለት ጥቅም አላት፣ አጎንብሼ ከመውጣት ትታደገኛለች፡፡ ነገር ካላማረኝ፤ ደጃፍ ሆነው ሲጠሩኝ በርክክ ብዬ ደረቱን በኩራት እንደነፋሁ እወጣለሁ::ሳቅሁ፤ ሳቄ ውስጥ ‘ይሄ ሁሉ ለምን? የሚል መልዕክት እንዳለው የተረዳሁት ቆይቼ ነው፡፡”ከጉልበት በታች እያዩ መኖር የእኔ ሳይሆን የአንተ ዕጣፈንታ ነው፡፡ ምክንያቱም ጫማህን የማሳየት ፍላጎትህ የሰው መጫሚያ ስመህ እንድታድር ያስገድድሃል፡፡ትክ ብዬ አየሁት፣ የፊቱ እወራረድ እንደ ግሪኮቹ አማልክት ሰልካካ በመሆኑ ከአፉ የሚወጡትን መጥፎ ነገሮች ከተፈጥሮው ጋር ያልተዋሃዱ ባዕድ ያደርግበታል፡፡“ተንበርክኮ በኩራት፣ ከአጭር ደጃፍ መውጣት አንተ የጀመርከው አይደለም::ዝም ባለ ገፅታ ቀና ብሎ አየኝ፡፡ናፖሊዮን በግዞት ኢልባ ደሴት ላይ በቆየበት ወራት ይሄንኑ ሲያደርግ ነበር፡፡ ደሴት አስተዳዳሪው በናፖሊዮን ኩራት ተበሳጭቶ አጎንብሶ እንዲወጣ በሩን ቆርጦ አሳጥሮበት ነበር፡፡ ናፖሊዮን ግን ከማጎብደድ መንበርከክን መርጦ በኩራት ደረቱን እንደነፋ ከቤቱ ይወጣ ነበር።”እኔን ትቶ ጭጋጉ ላይ የተመሰጠ መሰለ። ጥቂት በዚህ ሁኔታ ከቆየ በኋላ ድንገት እንደመባነን ብሎእባ ዲሪባ፣ አራጣ በሊታው።”ወዳተኮረበት መለስ ስል የተቆለለ ዳመና የመሰለ ጋቢ በጭጋግ ውስጥ ሲንሳፈፍ ተመለከትኩ:: ፊታቸውን ወደ ማሪያም ጌተክርስቲያን መልሰው እየተሳለሙ ነበር።

Related Articles

ቤባንያ ገፅ ፲፪

“ቋ!ቋ!ቋ!ቋ!…" “ምን ሆንሽ አመቴ!" አንድ ጥግ ላይ ተጎዝጉዞላት የተኛች አሮጊት ናት፡፡ “ምን ሆንሽ?” “ጥለውኝ ሄዱ" ባለፈውም የሰጠችው ምክንያት ነው:: “ጅብ ሊያስበሉኝ እዚህ...

ቤባንያ ገፅ ፲፪

“ቋ!ቋ!ቋ!ቋ!..." “ምን ሆንሽ አመቴ!" አንድ ጥግ ላይ ተጎዝጉዞላት የተኛች አሮጊት ናት፡፡ “ምን ሆንሽ?”“ጥለውኝ ሄዱ" ባለፈውም የሰጠችው ምክንያት ነው:: “ጅብ ሊያስበሉኝ እዚህ...

ቤባንያ ገፅ ፲፩

በመጀመሪያ ኬኦስ ነበረ፣ የማይጨበጠውና ዉጥንቅጡ ኬኦስ የረጋቸውን ምድር(ጂኦን) ወለደ:: "እንዴት?" አይባል የሚያሰኘው የእኔ ከምንም ውስጥ መገኘት ነው፡፡ ሃይፒሪዮን ፀሐይን፣ ጨረቃንና...

Comments

0 Comments

Submit a Comment

Your email address will not be published. Required fields are marked *